Wednesday, March 30, 2016

በ እንተ “ማኅበረ ቅዱሳን”: ክፍል_2


 በ ፒዲኤፍ ለማንበብ ይህንን ይጫኑ


እውን ማኅበረ ቅዱሳን ለ ቤተክርስቲያን  ስጋት ወይስ አቃቤ?
በቤተክርስቲያኗ ህግ መሰረት ማህበረ ቅዱሳን ተፈቀደለት መስመር ከወጣ፤ መስተካከል ያለባቸውን ጉዳዮች በዝርዝር አውጥቶ ማየትና የእርምት እርምጃ መውሰድ የሲኖዱሱ ጉባኤ ስልጣን ነው፡፡ ይህ ከሆነ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተክርስቲያኗ ስጋት የሚሆንበት አንዳችም መንገድ አይታየኝም፡፡ ከዚህ ባለፈ ከ ሲኖዶሱ እውቅና ውጭ በተለያዩ አካላት “ሾላ በድፍን” የሚደረጉ ዘመቻዎች የምዕመናንን ሰላም ከማወክ ያለፈ የረባ  ፋይዳ ይኖራቸዋል ብዬ አላስብም፡፡ በሌላ በኩል ግን ጥንታዊ ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ለማደስ በሚል ተልዕኮ በየቀኑ ለሚፈለፈሉ ምዕራብ ወለድ ሃይማኖቶች ከሆነ አሁንም ቢሆን ማኅበረ ቅዱሳን ስጋት ነው፡፡

Monday, March 28, 2016

በ እንተ “ማኅበረ ቅዱሳን”: ክፍል_1

(ትዝብትና ነፃ አስተያየት)
                  ( ዘላለም ጥላሁን_ zelatilahun@yahoo.com)
ማኅበረ ቅዱሳን ማን ነው? መች ተመሰረተ? ዓላማው ምንድን ነው? ቤተክርስቲያን ምን አበረከተ?   ብፁዕ አቡነ ማቲያስ ለምን ጠሉት? የሁሉም ቀስትስ ለምን ወደ ማኅበረ ቅዱሳን አነጣጠረ? እውን ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተክርሰቲያን ስጋት ወይስ አቃቤ?
(የውጭ አካላትን ጣልቃ ገብነት ለጊዜው ተወት አድርገን እስኪ መረጃ እያጣቀስን ወደ ውስጥ እንመልከት)
ቅድመ ታሪክ (ማኅበረ ቅዱሳን ማን ነው?): መተከልና ጋምቤላ መንደር ምስረታ፣ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የተማሪዎች የፅዋ ማኅበራትና የብላቴ ዘመቻ ማኅበረ ቅዱሳን መመስረት ትልቅ ድርሻ ቢኖራቸውም ብፁዕ አቡነ ጎርጎሪዎስ ካልዕ እና ብፁዕ / አቡነ ገብርኤል ወጣቶችን ሰብስቦ ከማስተማር ወደ አንድ የማኅበር ስያሜ እስከ ማምጣት ድረስ ያደረጉት ተጋድሎ ለማኅበሩ ቀጥ ብሎ መቆም መሰረት መሆኑን በጊዜው የነበሩ አባላት ሁሌም የሚናገሩት ሃቅ ነው1፡፡ በተለይ እምነቱን በእነ ሌሊንና እስታሊን ፍልስፍና ቀይሮ ሶሻሊስት አብዮት ጨርቁን ጥሎ በከነፈው ትውልድ መሃከል ስለ አብያተ እምነት የሚቆረቆር ትውልድ መኖሩ ነበር እኒህን አባቶች  “ ልጆቼ እኛ እናንተን መፈለግ ሲገባን እናንተ እኛን ፈልጋችሁ መጣችሁ፣ ንፍሮ ቀቅለን፣ አዳራሽ ባይኖረንም ድንኳን ጥለን እናስተምራችኋለን1,2,3,4 ብለው እንዲቀበሏቸው ያደረጋቸው፡፡ 

Friday, March 25, 2016

ለ "አንቺ ያለኝ ፍቅር"


ለፍቅርሽ ጥልቀት
ሰብዕናሽ ምጥቀት፤
ብራና ዳምጬ
ቃላትን መርጬ
ብዕሬን ጨብጬ፤
በሰከነ መንፈስ~ልፅፍ አስብና
ፈዝዠ እቀራለሁ~ሐሳብ ሁሉ መና
ማይጨበጥ ነፋስ~የቅዠት ደመና

Friday, March 18, 2016

አድዋ


ወይ አንቺ አድዋ!
የጥቁር ህዝብ ትንሳኤዋ!
በኩረ ነፃነት ምሰሶዋ!

የደመና ጥግ የሰማይ ክሳድ
የሐበሻ ዘር የወኔ ሞረድ
አፍሪካ ጭቁን የነፃነት በር
መክፈቻ ቁልፏ ይቻላልድር
የማንዴላ ኃይል የሉተር ህልም
መነሻ ሃሳብ ትንቢተ ዓለም
አድዋ አንቺ ነሽ
የሐበሻ ዘር በደም የፃፈሽ