በሐይማኖትና በዘር ጉዳይ ከእንግዲህ አልፅፍም ብዬ ለራሴ ቃል ብገባም፣ የጉዳዩ አሳሳቢነት ህሊናዬን ሰላም ነሳኝ መሞነጫጨር ጀመርሁ፡፡ ትናንት ማታ 8 ሰዓት ላይ ይህን ጉዳይ በገፄ ከለጠፍሁ በኋላ ብዙ መልክቶች በተለያዬ መልኩ ወደእኔ ደርሰዋል፡፡ ብዙዎቹ ቅንነት የሞላባቸው ናቸው፡፡ ሊቁን ለማገዝ የሚጠይቁም አሉ (መጨረሻ ላይ ሂሳብ ቁጥራቸውን አስቀምጣለሁ፣ ዘላቂ መፍትሔ ባይሆንም)፡፡
ወደ ጉዳዩ ከማምራታችን በፊት፣ ሁላችንም ከአሸናፊው እውነት ጋር እንሆን ዘንድ፣ ዛሬ ጥዋት አንድ ወዳጄ በአስተያይት ማስፈንጠሪያው ላይ ያስቀመጣትን የማህተመ ጋንዲን ጥቅስ አይተን እንለፍ፡
‹‹በምድር ላይ ብቻህን ብትቀር እንኳን ከግፈኞች ጋር አትተባበር። ዓለም ዓይኗን ብታቀላብህ አንተ ግን ፈገግታህን ለግሳት፡፡ አትፍራ፡፡ በልብህ ውስጥ ያለውን የእውነት ድምፅ ብቻ ታመን፡፡ ያ ድምጽ እንዲህ ይላል:- ባለንጀራህ፣ ሚስትህ፣ ዘመዶችህ፣ ጳጳስህ ሁሉም ቢተውህ ለምትኖርለትና ልትሞት ለተዘጋጀህበት እውነት ብቻ መስክር፡፡ የመኖር ትርጉሙ ይህ ነውና›› ማኅተመ ጋንዲ






