Thursday, August 16, 2018

ከነፃው ፕሬስ ፋና-ዎጊዎች


(በቅዱስ ሃብት በላቸው)
ነሃሴ 9 ቀን በኢትዮጵያ የነፃ ፕሬስ ታሪክ ፋና-ወጊ ተብለው በግንባር ቀደምትነት ከሚጠቀሱት ጋዜጠኞች መካከል አንዱ የሆነው የመብሩክ/መብረቅ ጋዜጣ አሳታሚና አዘጋጅ የነበረው ጋዜጠኛ ወርቁ ዓለማየሁ ከዚህ ዓለም በሞት የተለየበት ዕለት ነው።ትንሿ ትግራይ!” በሚል ርዕስ በአንድ መንግስታዊ ተቋም ውስጥ ከላይ እስከታች የተሰገሰጉትን የአንድ ብሔር ሰዎች በማስረጃ ማጋለጡን ተከትሎ ድንገት ታፍኖ እስር ቤት ተጥሎ የነበረው ጋዜጠኛ ወርቁ፣ ከእስር ቤት እንደወጣ ነበር እስከወዲያኛው ከዚህ ዓለም በሞት የተለየን።

Monday, August 13, 2018

‹‹ፍቅር›› ወይስ ‹‹ፍትህ›› የትኛው ይቀድማል?



ሰልጥነናል፣ ደሞክርሰናል፣ አድገናል እንላለን እንጂ ቁልቁል እየተምዘገዘግን ነው፡፡ ለአንድ ማህበረሰብ የእድገትም ይሁን የስልጣኔ መሰረት ለዘመናት ያካበተው የአስተሳሰብ፣ የሀይማኖት፣ የባህል እና የሞራል እሴት ነው፡፡ ይህ እሴት በዘመን መንገድ ውስጥ ተናደ፡፡ የ60ዎች ትውልድ በማህበረሰቡ ውስጥ የነበሩ የመተማመን ድልድዮችን ሰብረው፣ የመጠራጠርን ግንብ ሰሩ፡፡ በ60ዎች ከተፈለፈሉት የመደብ ተጋዮች በህይወት ተርፎ በትረ መንግስቱን የጨበጠው ‹‹ትህነግ›› የተራረፉ ድልድዮችን ሰባበራቸው፡፡ አንዱ አንዱን በአይነቁራኛ መከታል ጀመረ፡፡ አጥሩ እየጠነከረ ሂዶ ዘመን በሚሻገር የዘር አጥር ታጠረ፡፡ ትህነግ ‹‹ ንግበር በአርያነ…..›› ብሎ የፈጠራቸው የየብሔሩ ድርጅቶችም ድልድይ አፍርሶ ግድግዳ መጠገን ላይ ተጠመዱ፡፡

Saturday, August 11, 2018

የልጅነት ትዝታ


ይችን ልጅ ሳይ ልጅነቴ ትዝ አለኝ፡፡ ከልጅነቴ ውስጥ ደግሞ የአራተኛ ክፍል የሳይንስ መምህር ትዝ አሉኝ፡፡ አንድ ቀን የሳይንስ መምህር አዳፋ ካቦርታቸውን እና እንደ ምድር ወገብ መሃል ለመሃል የተሰነጠቀች ባርኔጣቸውን ለብሰው ወደ ክፍል ገቡ፡፡
እንደምን አደራችሁ ልጆች
ሁላችንም ተነስተንእንደምን አደሩ መምህር
ቁጭ በሉ
እሺብለን ቁጭ!
ምን አለበትእንደምን አደሩስንላቸውእግዚሃር ይመስገንወይምደህና ነኝቢሉን!...አላሉንም..... ቀጥታ ገጣባ አህያ ወደ ሚመስለው ብላክ ቦርድ ሄደውሳይንስብለው ጻፉ፡፡ ቀጥለውም የሰሌዳው ጠርዝ አካባቢ በዲያጎናል አስምረው ቀን ፃፉ፡፡ 

Wednesday, July 4, 2018

ሻምበል አስረስ ገላነህ ብዙነህ [ጎጃሜው]

                                          (የግፍ ጥግ የተፈፀመበት የጦር መኮንን)
ለመጀመሪያ ጊዜ በአማራ ህዝብ ላይ እየተሰራ ያለውን አሻጥር ፊት ለፊት የተጋፈጠ የጦር መኮንን ይህ ሰው ይመስለኛል፡፡ ‹‹ሳሞራ››ን ፊት ለፊት የተጋፈጠ፣ ባህርዳር በተደረገው ስብሰባ ከእነ በረከት እና ህላዌ ጋር ‹‹በአማራ ስም አትነግዱ›› ብሎ ፊት ለፊት የተፋጠጠ የመጀመሪያው ሰው ይህ ይመስለኛል፡፡ በዚህም ድርጊቱ ‹‹ ጎጃሜው›› የሚል ቅፅል ስም እንደተሰጠው ባለታሪኩ ይገልጻል፡፡ በዝሆኖች ጥርስ የተነከሰበት ይህ ቆፍጣና የጦር መኮንን የማታ ማታ ‹‹ የአልጋ ቁራኛ›› የሚያደርገው ግፍ፣ እላዩ ላይ ነዳጅ አርከፍክፎ ፓርላማ ፊት ለፊት እራሱን እንዲያቃጥል ያስወሰነው መከራ ተፈፀመበት፡፡  ይህ ሰው ‹‹የካድሬው ማስታወሻ›› የተሰኘ ግለ ታሪክ 2005 ዓ.ም አካባቢ ለንባብ አብቅቷል፡፡ መፅሃፍ አንብቤ ያለቀስኩበትን፣ ከመጠን በላይ ልቤ የተነካበትን ጊዜ አላስታውስም፡፡ የዚህን ጀግና ግለታሪክ ሳነብ ግን አልቅሻለሁ፡፡ በማልቀስ ብቻ አላለፈም፣ ከውስጥ የሆነ ተስፋ ሲሰበር ይታወቀኝ ነበር፡፡ የጭካኔን ጥግ ያየሁበት ትርክት ስለሆነ!

Tuesday, July 3, 2018

የሀገሬ መንገድ

                              (Photo: Google)
ወገኛው በኃይሉ ገ/መድህን ‹‹የእኔ እና የሀገሬ ነገር መሬት አልረገጠም›› ብሎ ነበር ከአንድ ሁለት ሶስት ሳምንት በፊት፡፡ አንዳንዱ በቃ ኢትዮጵያ መቼም ወደማይቀለበስ የዲሞክራሲ አስተዳደር ተሸጋገረች ብሎ ይዘምርና ትንሽ ቆይቶ ‹‹እነ እንትና አለቀላችሁ!፣ እነ እንትና እንዲህ መደረግ አለባቸው፡፡ እንዲህ እንዳደረጉንማ በዋዛ አንለቃቸውም፡፡ እንትና ይታሰር፡፡ እንትና ይመርመር! እንትና ይሰቀል››  እያለ ይፎክራል፡፡ ወገን ዲሞክራሲ እና ፉከራ አብሮ አይሄድም፡፡ ዲሞክራሲ ‹‹ከፍፁም ይቅርታ እና መቻቻል የሚፈጠር የማህበረሰብ ደልድይ ነው››፡፡  የሆነ ቦታ ላይ ሁሉንም ነገር በይቅርታ ማራገፍ ካልተቻለ፣ ቂምና በቀል ጅረት ነው-ማቆሚያ የለውም፡፡ ጅረቱ ውቅያኖስ ውስጥ ተጠራቅሞ አንድ ቀን ነፋስ ሲንጠው፣ ማዕበሉ የሚያመጣው ቀውስ ምን ያህል ከባድ እንደሆነ በትንሹም ቢሆን ቀምሰነዋል፡፡ 

Monday, July 2, 2018

ጠ/ሚ/ዶ/ር አብይ አህመድ በሀገሪቱ ለተደረጉ የድጋፍ ሰልፎች ያቀረቡት ምስጋና


የተከበራችሁ የሀገራችን ህዝቦች ሆይ!
ምስጋና ከሚቀበል ሰው ይልቅ ምስጋና የሚሰጥ ታላቅ ነው! ያለ ጥርጥር ይህንን እንረዳለን፡፡ ባለፉት ሶስት ወራት በሀገራችን እየታየ ያለው የለውጥ ጭላንጭል፣ አሁን የሀገራችን ህዝብ እየሰጠን ካለው ወሰን አልባ ድጋፍ እና ፍቅር ጋር የሚወዳደር እንዳልሆነ ብንገነዘብም መንግስት ይሄንን ድጋፍ ፍቅር ክብር እና አለኝታነት ለተሰሩ ስራዎች እንደተሰጠ ምስጋና ብቻ ሳይሆን በቀጣይ እንሰራቸው ዘንድ ለሚገቡን በርካታ ስራዎች ተግባራዊነት የተላለፈ የአደራ መልእክት እንዲሁም የአጋርነት ማሳያ አድርጎ በመቁጠር ከምን ጊዜውም በላይ በፍጹም ቁርጠኝነት እና ትጋት ለማገልገል በጽናት ይሰራል፡፡

Friday, June 29, 2018

ይድረስ ለባህርዳር የድጋፍ ሰልፍ አስተባባሪ ኮሚቴ

(ጥብቅ ጥንቃቄ ስለማድረግና መፍትሄዎችን ስለመጠቆም (ምሳሌ የ 5-ለ5 አደረጃጀት)
በሩቁ ሁኖ የፍርሃት ድባብ መልቀቁ ብቻ መፍትሔ አልመሰለኝም፡፡ ሰልፉ እውን መሆኑ ካልቀረ ጥንቃቄው ላይ መነጋገር መልካም ይመስለኛል፡፡ ስለዚህ ከአዲስ አበባው የድጋፍ ሰልፍ ላይ ያየኋቸው ክፍተቶች ባህርዳር ላይ እንዳይደገሙ ቅድመ ጥንቃቄ እንዲደረግ በትህትና አመለክታለሁ፡፡

Saturday, June 16, 2018

ምን ነበር በደልህ?


(ለመ/ር እንደስራቸው አግማሴ)
ምን ቃል ተረፈና፣ በምን ልዘንልህ
የትርጓሜውን ስንክሳር፣ እልፍ ቅኔ ይዘህ ታስረህ፣
መቼ ነበር የጨለመ፣ ስንት ጥዋት ነጋ?
ስንት ክረምት ቆጠርህ፣ አለፈ ስንት በጋ?
ስንት ይሆናል እድሜህ፣ ከልጅነት እስከ አሳር?
ሳትኖር የኖርኸው ተቀንሶ፣ ያለፈው ክረምት ሳይቆጠር?
መቼ ይሆን ያንተ ጥዋት፣ መቼ ይሆን ያንተ በጋ?
ፍትህ በደጅህ ደርሶ፣ ጨለማ ቀንህ የሚነጋ?

ዶ/ር አብይ አህመድ በአለቃ ገብረሃና አምሳል


ምዕት ዓመት ተሻግረው በትውልድ ልብ የማይጠፉት ባለምጡቁ አእምሮ፣ ሊቅ፣ ፈላስፋ እና ጥበበኛው አለቃ ገብረሃና እንደ ልማዳቸው መንገድ ላይ ሲያዘግሙ በርቀት ሰዎች ተጣልተው ሲሰዳደቡ ያያሉ፡፡ በሀገሬው ልማድ ሰው ተጣልቶ እያዩ ማለፍ ነውር ነውና አለቃ ወደ እነሱ ሄዱ፡፡ አለቃ ቀረብ እያሉ ሲሄዱ ጠቡ እየበረታ ከስድብ ወደ ግልግል ደረሰ፡፡ አለቃም መሃል ገብተው ሁለቱን ወደ ተቃራኒ አቅጣጫ እየገፉ ጠቡን ለማብረድ ሞከሩ፡፡ የተጣሉት አንድ በእውቀቱ አንቱ የተባለ ሊቅ እና ከእውቀት አርባ ክንድ የራቀ ሰው ነበሩ፡፡ ከእውቀት ነፃ የሆነው ሰው ሊቁን ‹‹አንተ ደደብ…አንተ ደደብ›› እያለ ይሰድበዋል፡፡ ‹‹ አለማወቅ ነፃነት ይሰጣል›› እንደሚሉት ማለት ነው፡፡ ወደ ጠቡ ቦታ አንድ ሌላ ሰው መጣ፡፡ የአለቃን ሁኔታ ተመለከተና ‹‹ አለቃ ምን እያደረጉ ነው?›› ሲል ጠየቃቸው፡፡ የቅኔ ሊቁ እና ፈሊጠኛው አለቃም ‹‹ስድብ ቦታውን ስቶብኝ …ቦታ ቦታውን እያስያዝሁ ነው›› አሉ ይባላል፡፡