Friday, November 16, 2018

የሊቀ ስዩማን መዝገቡ ጉዳይ እና የአዊ ሀገረ ስብከት ውዝግብ-ክፍል ሁለት



በሐይማኖትና በዘር ጉዳይ ከእንግዲህ አልፅፍም ብዬ ለራሴ ቃል ብገባም፣ የጉዳዩ አሳሳቢነት ህሊናዬን ሰላም ነሳኝ መሞነጫጨር ጀመርሁ፡፡ ትናንት ማታ 8 ሰዓት ላይ ይህን ጉዳይ በገፄ ከለጠፍሁ በኋላ ብዙ መልክቶች በተለያዬ መልኩ ወደእኔ ደርሰዋል፡፡ ብዙዎቹ ቅንነት የሞላባቸው ናቸው፡፡ ሊቁን ለማገዝ የሚጠይቁም አሉ (መጨረሻ ላይ ሂሳብ ቁጥራቸውን አስቀምጣለሁ፣ ዘላቂ መፍትሔ ባይሆንም)፡፡
ወደ ጉዳዩ ከማምራታችን በፊት፣ ሁላችንም ከአሸናፊው እውነት ጋር እንሆን ዘንድ፣ ዛሬ ጥዋት አንድ ወዳጄ በአስተያይት ማስፈንጠሪያው ላይ ያስቀመጣትን የማህተመ ጋንዲን ጥቅስ አይተን እንለፍ፡
በምድር ላይ ብቻህን ብትቀር እንኳን ከግፈኞች ጋር አትተባበር። ዓለም ዓይኗን ብታቀላብህ አንተ ግን ፈገግታህን ለግሳት፡፡ አትፍራ፡፡ በልብህ ውስጥ ያለውን የእውነት ድምፅ ብቻ ታመን፡፡ ድምጽ እንዲህ ይላል:- ባለንጀራህ፣ ሚስትህ፣ ዘመዶችህ፣ ጳጳስህ ሁሉም ቢተውህ ለምትኖርለትና ልትሞት ለተዘጋጀህበት እውነት ብቻ መስክር፡፡ የመኖር ትርጉሙ ይህ ነውና›› ማኅተመ ጋንዲ
ክፍል አንድ ላይ ለመነካካት እንደሞከርሁት የአዊ ሀገረ ስብከት ውዝግብ የጀመረው ብፁዕ አቡነ ቶማስ በተሾሙ ማግስት ነው፡፡ የዞኑ ምዕመናኖች እና የዞኑ አስተዳደር ለሲኖዶስ ባቀረበው ጥያቄ መሰረት፣ በቅርብ ጵጵስናን ከተቀበሉ አባቶች ውስጥ አንዱ የሆኑት አቡነ ቶማስ ተሾሙ፡፡ አቡነ ቶማስ ከአቡነ ማርቆስ (የምስራቅ ጎጃም ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ የነበሩት) ጋር ከመንፈሳዊነት ያለፈ የቀረበ ወዳጅነት እንዳላቸው ብዙዎች ይናገራሉ፡፡ ባለፈው አመት በነበረው የጥቅምት ሲኖዶስም ላይ የነበራቸው አሰላለፍ ይህን አጉልቶ ያሳይ ነበር፡፡ እኒህ አባት ወደ ዞኑ ሲላኩ ብዙ ምዕመን ደስተኛ አልነበረም፡፡ ስለ እሳቸው ግለሰባዊ ማንነት ያተኮሩ ነገሮች በማህበራዊ ሚዲያ ተሰራጭተው ነበር (እሱን እዚህ ላይ ማንሳት ተገቢ ነው ብዬ አላስብም፡፡) ከሀይማኖት ዶግማ ጋር በተያያዘም ገና በጥዋቱ ብዙ ነገሮች መወራት ጀምረው ነበር፡፡ አቡነ ማርቆስ ከሚታሙበት ‹‹የቕባት አስተምህሮ›› ጋር አብረው ይነሱ ነበር፡፡

ጥቅምት 2010 . ገና በአፍላ ሹመታቸው ከሀገረ ስብከት አብረዋቸው ለሲኖዶስ ስብሰባ ከመጡት መካከል አንዱ የካህናት አገልግሎት ሃላፊው ሊቀ ስዩማን መዝገቡ ነበሩ፡፡ ሊቀ ስዩማን ስለውሏቸውና ሀገረ ስብከቱ ላይ ከባድ ችግር መፈጠሩን እያወሩኝ ወደቤት ሄድን፡፡ ሊቀጳጳሱ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባል ነገር መስማትም ማየትም እንደማይፈልጉ፣ እኔም መድረክ ላይ ወጥቼ በአደባባይ ማኅበሩን እያጥላላሁ ካልሰበክሁ፣ የእንጀራ ገመዴ ሊበጠስ እንደሚችል አስጠንቅቀውኛል አሉኝ፡፡ ‹‹የባሰ አለ፣ ሀገርህን አትልቀቅ›› አሉ፡፡ ኤኔታ አሳዘኑኝ፡፡ ቤት ደረስን፡፡ ቤት ያፈራውን ትንሽ ምግብ ቀምሰው ወደ ማታ ፀሎት ገቡ፡፡ ፆሎታቸውን ስንት ሰዓት እንደጨረሱ አላውቅም፡፡ እኔ ተኝቻለሁ፡፡ ከሌሊቱ ስምት/ዘጠኝ ሰዓት አካባቢ በሩ አልከፈት ብሏቸው ሲታገሉ ነቃሁ፡፡ ውሃ ፈልገው ነበር፡፡ ፊታቸውን ታጥበው ወደ ጸሎት ገቡ፡፡ እኔ ተመልሸ ተኛሁ፡፡ ጥዋት ስነሳ ፀሎት ላይ ናቸው፡፡ በጥዋቱ ግርምት ውስጥ ገባሁ፡፡ ‹‹የአሰም እና የስኳር በሽተኛ ሆነው፣ የቤተሰብ አስተዳዳሪ ሆነው፣ አገልጋይ ሆነው፣ ስብሰባ ውለው›› ዛሬም ለፀሎት ያላቸው ትጋት በጣም ገረመኝ፡፡

ይች ሀገር በእነማን ትጋት እንደምትኖር በሙሉ ልቤ ያመንኩት በአንድ ወቅት ዋልድባ እና ዱር አንበሳ ገዳም ላይ በነበረኝ ቆይታ ባየሁትና በተረዳሁት ነገር ቢሆንም፣ ከተማ ውስጥ እየኖሩ በፀሎት የሚተጉ አባቶችን ሳይ ውስጤ በተስፋ ይሞላል፡፡ በአንጻሩ ባዶነቴን አያለሁ፡፡ በዚህ ዓለም ከመኖር ባሻገር ማሰላሰል እጀምራለሁ፡፡ (በነገራችን ላይ፣ ይህ እምነቴ ይመስለኛል 2004 . የዋልድባ መሬት ሲታረስ ከሁሉ ቀድሜ ጉዳዩን ጋዜጣ ላይ በማውጣት ውጊያውን የጀመርሁት፡፡ በወቅቱ የነበረኝ ትዝብቴና ፍራቴ ትንቢት ሁኖ ነሀሴ 2004 . የደረሰውን ሁነት አስተናግደን እዚህ ደርሰናል፡፡ ጋዜጣው ላይ የወጣው ፅሁፍም ለታሪክ ተቀምጧል፡፡ እኔም ዛቻውን አልፌ ዛሬ አለሁ፡፡) ዋናው መልዕክቴ ‹‹ ቤተክርስቲያን እና እውነትን የሚታገሉ ሰዎች ከመውድቅ አይድኑም›› የሚል ነበር፡፡ ይህ ነገም ይቀጥላል፡፡ ፃድቅ ባልሆንም አምናለሁ፡፡
ወደ ቀደመ ነገራችን ስመለስ፣ ኤኔታ ወደ አዊ ከመመለሳቸው በፊት ስጉዳዩ መወያየት ጀምርን፡፡
‹‹
ያሉኝን ካላደርግሁ፣ መባረሬ ነው›› አሉኝ
‹‹
እና ምን አሰቡ››
‹‹
የመጣውን በፀጋ እቀበላለሁ እንጂ፣ ከህሊናዬ አልጣላም፡፡ የውሸት ቃልስ እንዴት ብሎ ከአፌ ይወጣልኛል›› አሉ
‹‹
ልክ ነዎት ኤኔታ፣ መሆን ያለበት እንደዚያ ነው፡፡ በተቻለ መጠን ነገሮችን በውይይት ለመፍታት ሞክሩ፡፡ ካልሆነና ነገሩ ከከፋ ከተባረሩ ወደ ሌላ ሀገረ ስብከት ሄደው ይስሩ››
‹‹
አይ ዘሌ የእኔማ ችግር የለውም፣ የእነዚህ ነፍሳቶች ነገር ነው ወገቤን የያዘኝ››..

በልጅነቴ የሰማሁት የጎጃም ገበሬዎች ሲከፋቸው የሚሸልሉት ሽለላ ‹‹ኧረ ልጅ ማሰሪያው፣ኧረ ልጅ ገመዱ፤ ጎጆማ ምን ይላል ጥለውት ቢሄዱ›› የሚለው ትዝ አለኝ፡፡ እውነታቸው ነው፡፡ እሳቸው የትም ቦታ ሄደው ማገልገል የሚችሉ ሊቅ ናቸው፡፡ ቤተሰብን ይዞ መሰደድ ግን ከባድ ነው፡፡ ተለያዬን፡፡ እንደጠበቁት ከሁለት ወር በኋላ ተባረሩ፡፡ ከመባረራቸው በፊት ‹‹ከካህናት አገልግሎት ሃላፊነት ወደ ንብረት ክፍል›› ተዛውረው እንዲሰሩ ደብዳቤ ተሰጣቸው፡፡ ስራውን እምቢ አላሉም፣ ነገር ግን ከአለባቸው የአሰም ህመም ጋር ያስቸግረኛል ብለው ቅሬታ አቀረቡ፡፡
ሀገረ ስብከቱም ጥር 8 2010 . በተፃፈ ደብዳቤ ‹‹ትኩረትዎ ከቀድሞውም ወደ ስራ አለመሆኑን ተግባርዎ ይመስክራል›› የሚል የማሸማቀቂያ ሀረግ ባለው አንድ ገፅ ወረቀት ‹‹ህመምዎን እንዲያስታምሙ በጡረታ ተሰናብተዋል›› ተብለው 40 ዓመታቸው ተሰናበቱ፡፡ (ደብዳቤው ተያይዟል)

ነገሩን ለማሳጠር፣ ጉዳዩን ወደ ህግ ወሰዱት፡፡ ብፁዕ አቡነ ቶማስም ጠበቃ አቁመው ሞገቷቸው፡፡ የኢፌዲሪ መንግስት የሚንሰትሮች /ቤት መጋቢት 2007 . ከሃይማኖትና በጎ አድራት ሰራተኞች ግንኙነት ጋር በተያያዘ ባወጣው ደንብ ላይ አንቀፅ 3 ንዑስ አንቀፅ 1 ላይ የተጠቀሰው ‹‹ከመንፈሳዊ አገልግሎት ጋር የተገናኘ›› የሚለው እና አንቀፅ 3 ንዑስ አንቀፅ 4 ላይ የተጠቀሰው ‹‹ከአስተዳድራዊ አገልግሎት ጋር የተገናኘ›› የሚለው ዳኞችን ውዝግብ ውስጥ ከተተ፡፡ በተመሳሳይ ጉዳይ ላይ የተወሰነ የሰበር ችሎት ውሳኔም አገኘሁ፡፡ መካሰሱን ብዙ አልወደድሁትም፡፡ በሽማግሌ ብትታረቁ መልካም ነው ብዬ ሃሳቤን አካፈልሁ፡፡ ሽማግሎች ክሱ ይዘጋ ብለው ሊቀጳጳሱን ቢሸመግሉም፣ ‹‹ጠበቃ የቀጠርሁበትን 15000 ብር ይክፈለኝና ይዘጋ›› ብለው መለሱ፡፡ ጉዳዩ ‹‹አዋጁና ደንቡ›› ባለው አወዛጋቢ አንቀጽ አሁንም ዳኞች እጅ ከርሟል፡፡ በመሃል ሊቀ ስዩማን ፍትህን ፍለጋ አባይን ተሻግረው ለስራ አስኪያጁ ለአቡነ ዲዎስቆሮስ ይግባኝ አሉ፡፡ ውሃ የሚያነሳ መልስ ሳያገኙ ከሸዋ ወደ አዊ ተመለሱ፡፡ በእኔ አረዳድና ካነጋገርኋቸው የቅርብ የህግ ባለሙያ ጓዶቼ ትንተና አንጻር፣ ሊቀ ስዩማን ይሰሩት የነበረው ‹‹የአስተዳደር ስራ ስለሆነ ህግ ጣልቃ መግባት ይችላል›› አሉኝ፡፡ ውሳኔው በቅርብ ይሆናል ስላሉኝ፣ እሱን አብረን እንጠብቅ፡፡

የሊቀ ስዩማንን ጉዳይ እንደ በረሃ መንገድ ያረዘምሁት፣ በእሳቸው ጉዳይ ዱካ የሌሎችን መተንበይ ትችላላችሁ ብዬ ነው፡፡ ሊቀ ስዩማን ለአዊ ህዝብ ምን ማለት እንደሆኑ ብዙ ሰው ያውቀዋል፡፡ ለእሳቸው ይህ ከሆነ የሌሎችን መገመት አይከብድም፡፡ 

አቡኑ ባለፉት 12 ወራት ብዙ ሰዎችን ከስራ አባረዋል፡፡ ብዙዎችን ከሰዋል፡፡ የማህበረ ቅዱሳን አባላትን ከቢሮአቸው አባረዋል፡፡ የማህበረ ቅዱን አባል የሆነን ሰው የንስሃ አባት የያዘ ካህን ከአገልግሎት ታግዷል፡፡ ከስርዓተ ቤተክርሰቲያን፣ ከዶግማና ከቀኖና ጋር የተያያዙ ብዙ ነገሮች ተጥሰዋል፡፡ ይህ ጉዳይ እያደር ምዕመኑንና ወጣቱን ወደ ሁለት ዋና ጎራ መክፈል ጀመረ፡፡ የአቡነ ቶማስ ደጋፊና የእሳቸው ተቃዋሚ በሚል ጎራ፡፡ ልክ አሁን አገሪቱ ላይ እንዳለው ነፋስ መሆኑ ነው፡፡
በአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ በማህበሩ አባላት፣ በመምህራን ላይ የማባረርና የማፈናቀል ጉዳይ፣ ከቅድስት አርሴማ ገዳም ጋር ተያይዞ ያለው የመነኮሳት ማባረር ጉዳይ እየባሰ ሲሄድ ከዞኑ 9 ወረዳዎች የተውጣጡ ምዕመናን ለዞኑ /ቤት አቤት አሉ፡፡ የዞን ሃለፊዎች በም/ቤቱ አዳራሽ ምዕመናኑን አነጋገሩ፡፡ ምዕመናኑ በጣም ብዙ ጉዳዮችን 12 ገጽ አጠናቅረው ያቀረቡ ሲሆን በመጨረሻም መደረግ ያለባቸውን 8 ነጥቦች አነሱ፡፡ ማንበብ ለምትፈልጉ ማስረጃው የተያያዘ ቢሆንም ያነሷቸውን ዋና ዋና ነጥቦችን አሳጥሬ ላንሳቸው፡
1) ከቤተክርስቲያን ዶግማ የሚቃረን ስብከት ሰብከዋል፡፡ ‹‹ ተሃድሶ፣ መናፍቃን፣ ቅባት የሚባል ነገር የለም›› እያሉ ሰብከዋል፡፡
2)
የመልካም አስተዳደር ችግር፡ ካህናትን፣ አስተዳዳሪዎችን እና መምህራንን አባረዋል፡፡
3)
መመህራን እንዳያስተምሩ ታግደዋል (ሊቀ ጠበብት ስጦታው፣ ሊቀ ስዩማን መዝገቡ፣ ሊቀ ሊቃውንተ ስምአኮነን ጠቅሰዋል)
4)
ወጣቱ ተሰባስቦ ስለቤተክርቲያኑ እንዳያውቅ አድርገዋል፡፡ በዚህም ምክንያት 72 ወጣቶች ወደ ጵሮቴስታንት እምነት ተቀላቅለዋል፡፡
5)
አቅም ያላቸውን የሀገረ ስብከት ሰራተኞች አባረው፣ ለቦታው የማይመጥኑ ሰዎችን መድበዋል፡፡
6)
የማህበረ ቅዱሳን አባላትን እንዲበተኑ አድርገዋል
7)
ማህበረ ቅዱሳንን ሲኖዶስ አግዶታል በማለት ምዕመኑ ላይ መንፈሳዊ መረበሽ ፈጥረዋል፡፡
8)
የገንዘብ ምዝበራ ተደርጓል
9)
ቅድስት አርሴማ አንድነት ገዳም 44 መነኮሳት ሲባረሩና ገዳሙ ሲመዘበር ዝምታን መርጠዋል፡፡
10)
ለሊቀ ጳጳሱ በቀን የሚታሰብላቸው 5- 30 የሚደርስ አበል በዝቷል………..እያለ ይቀጥላል ትግስት ካላችሁ ሙሉውን አንብቡት፡፡
የዞኑ አመራርም ጉዳዩን በጥንቃቄ አጢኖ ደብዳቤ ወደ ሀገረ ስብከቱ ፃፈ፡፡ ጎራው እየሰፋ፣ ዛቻውና ማስፈራሪያው በሁለቱም ጎራ እየከፋ ሄደ፡፡ በአቡነ ቶማስ ጎን ያሉ የተወሰኑ ሃብታሞች (በሚቀጥለው እመጣለሁ) ሌሎችን ማስፈራራት ጀመሩ፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ህዝቡ ጥቅምት 16 2011 . በስታዲዮም በመሰብሰብ ጩኸቱን ለዞኑ ሰላማዊ በሆነ መንገድ አሰማ፡፡ የአቋም መግለጫውን ይዘው ወደ አርባ የሚሆኑ ምዕመናን ለሲኖዶስ አቀረቡ፡፡ ጉዳዩ እልባት ሳያገኝ የጥቅምት ሲኖዶስ ተጠናቀቀ፡፡ በዞኑ ያለው ውጥረት እንደቀጠለ ቢሆንም፣ ሁኔታው ያላማረው የዞኑ አስተዳደር ‹‹ከዚህ በኋላ ለሚፈጠረው የፀጥታ ችግር ሃላፊነቱን ሀገረ ስብከቱ ይወስዳል›› በሚል ደብዳቤ ለፌደራል ተቋማትና ለክልል ተቋማት በግልባጭ አሳወቀ፡፡ (2 ገጽ ደብዳቤ ተያይዟል)፡፡
በሁለት ጎራ በተከፈለ ፍጥጫ፣ ግራ በተጋባ ምዕመናን እየተወዛገበ ያለው አዊ ዞን መፍትሔው ምን መሆን አለበት፡፡ 
ችግሩስ በዘላቂነት እንዴት ይፈታ?
(
በክፍል ሶስት እንወያያለን፡፡) ለጊዜው ግን ሊቀ ጳጳሱ ወደ ዞኑ ከመሄድ ቢታቀቡና ባሉበት ቦታ ቢቆዩ፣ ሽማግሎችና የዞኑ አመራሮች ጉዳዩን በሰከነ መንገድ ቢወያዩበት መልካም ነው እላለሁ፡፡
----------------------
--
መርዳት እንፈልጋለን ላላችሁ
ሊቀ ስዩማን መዝገቡ እስከዚያ የሂሳብ ቁጥር 1000159547055 የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ
-------------------------------------------------------
(
መሳሰቢያ፤ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን ማንነት ማወቅ ለምትፈልጉ፣ ከዛሬ 2 ዓመት በፊት ከፓትሪያርኩ ጋር ተፈጥሮ በነበረው ውዝግብ ወቅት የፃፍሁትን 3 ተከታታይ ክፍል በሚከተለው ሊንክ አንብቡ፡ (በእንተ ማኅበረ ቅዱሳን http://zelalemtilahun.blogspot.com/2016/03/blog-post_28.html)
ምልካሙን ሁሉ ያሰማን!
አሜን

ይቀጥላል

1 comment: