Sunday, December 24, 2017

አዲስ አበባ (በረራ)

እንዲህ ብሎ መጣፍ አሰኘኝ፡፡
የአዲስ አበባ ሰማይ ጎህ ሲቀድ፥ ካድሬም ቢሆን የሚያሳቅፈውን የታህሳስን ውርጭ እንደምንም ታግዬ ከምኝታዬ ታፋታሁ፡፡ፀጥ ባለው የአዲስ አበባ ሰማይ ስር፥ የሰንበት ቅዳሴ አድማሱን ተሻግሮ ከብርዱ ጋር የሚታገለውን የአማንያንን ልብ በሐሴት ይጠራል፡፡
"እምነ በሐ....ቅድስት ቤተክርስቲያን......አረፋቲሃ......"
;
ይቀጥላል፡፡
ከገደል ማሚቶው ቀጥሎ የሌላ ደብር ምስጋና የብርዱን ቆፈን እንደ ሰም ያቀልጣል፡፡ አማኒያን ነጠላቸውን መስቀለኛ አጣፍተው ውር ውር ይላሉ፡፡
አዲስ የሁላችንም ናት፡፡ የካድሬው፥ የወሬኛው፥ የሃብታሙ፥ የድሃው፥ የዘረኛው፥ የኢ-ዘረኛው፥ የለፍቶ አዳሪው፥ የአማኙ፥ የቀማኛው፥ የአሳሪው፥ የታሳሪው፥ የምሁሩ፥ የባዶ ጭንቅላቱ፥ የእግረኛው፥ የባለ ሐመሩ፥ የጦም አዳሪው፥ የሰክሮ አደሩ ከተማ ናት፡፡
አዲስ ሞትና ህይወት መሳ ለመሳ ተቻችለው የሚኖሩባት ፃድቅ ከተማ ናት፡፡ ቁራሽ ዳቦ ነጥፎበት በርሃብ የሚያጣጥር ብላቴና፥ ከሃብታም ኪስ የወደቀን ብር አግኝቶ "ጋሽ ብር ጥለዋል" ብሎ የሚሰጥባት ገዳም፡፡
500 ዓመት በፊት የዳሞቶች (ጋፋቶች) መዲና የነበረችው አዲስ አበባ አሁን 200 በላይ የሚሆኑ የዓለም ጎሳዎችን እንደ ጫጩት አቅፋ በምትሃት ታኖራች፡፡
(We heartily thank the extinct ancestors (damots) who gave this land)....ማለት ብንለምድስ?
የአሁኗ አዲስ አበባ (የድሮዋ በረራ) ዙሪያ ቤተመንግስታቸውን ተክለው ለነበሩት #አፄ_ዳዊት እና የዳሞት ወገኖቻችን መታሰቢያ ሐውልት ቢቆም ምን ይመስላችኀል?
የየረር ተራሮችን ሰንጥቀው ወደ አዲስ አበባ እቅፍ የተወረወሩት የፀሐይ ጨረሮች ከተማዋን ማሞቅ ጀምረዋል፡፡ አዲስ አበባ የቅዝቃዜ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ፥ የኑሮና የተስፋ ቆፈን በብርድ ልብስ ጠቅልሎ ያስተኛት ከተማ ናት፡፡ አዲስ ከጥዋት ጮራ ጋር አብራ መፈንደቅ የማትችል ህመምተኛ ምድር ናት፡፡ የሁላችንም ጓዳ ግን የእኔ ነሽ የሚላት ያጣች........
ልቀጥል........
;
አዲስዬ እየራቅሁ ነው፡፡ ስመለስ እቀጥላለሁ፡፡ ኔትወርክ ሲኖር፡፡


No comments:

Post a Comment